“It is not uncommon for people to spend their whole life waiting to start living.” ― Eckhart Tolle
ታላቁ ገጣሚ ጸጋዬ ገ/መድህን “አብረን ዝም እንበል” በተሰኘው ግጥሙ ውስጥ
“ተስፋ መቀነን ነው መቼም
የሰው ልጅ አይችለው የለም” ይለናል።
አንድም ህይወታችን ያለተስፋና እና ምኞት ነቅታ መጓዝ እንደማትችል ሲጠቁመን። በሌላ በኩል ደግሞ የሰውን ልጅ ማለቂያ የሌለውን ምኞት ሲያስዳስሰን ይመስለኛል። ህይወታችንን ብንቃኘው ደስታ ይሰጡናል ብለን ስንጠብቃቸው የነበሩት ነገሮች በእጃችን ሲገቡ እንዳሰብነው ደስተኛ ሳያደርጉን ይቀሩና ደግሞ ከፍ ወዳለ ሌላ ምኞት ያሻግሩናል።
“ይህንን ባገኝ ደስተኛ እሆን ነበር” የሁላችንም መፈክር አይደለም? ወይም የለመድነው የኑሮ ሂደት። ከላይ የሰፈረው የኤካርት ቶሌ አባባል ይህንን አኗኗራችን በደንብ ይገልጸዋል ብዬ አስባለው ። ሰዎች ኑሮን ለመጀመር እየጠበቁ ኑሮን ሀ ብለው ሳያጣጥሙ የእድሜያቸው ጀንበር ትጠልቃለች። ጥሩ ስራ ሲኖረኝ፤ ትዳር ስመሰርት፤ ይህንን ያህል ገንዘብ ሳገኝ፤ አላማዬን ሳሳካ ደስተኛ እሆናለው እያለን ለኑሮዋችን ቀጠሮ ስንሰጥ፤ ያሰብነው እስኪሳካ ደስተኛ ላለመሆን እየወሰንን ነው።
የሰው ልጅ ምኞት ማለቂያ የለውም። በጠየቅን ቁጥር ፈጣሪ ያልነውን ቢሰጠን እንኳን እንደሰው እረክቶ ለመኖር ይከብደናል። ለዚህ ነው ደስታችንን ነገ ከምናገኛቸው ነገሮች ጋር መቋጠር ዛሬን በሰመመን እንድንኖር የሚያደርገን። ያሰብኩት እስኪሳካ ደስተኛ መሆን አልችልም ማለት ነው “አስከዛው አልኖርም” ማለት ነው። የነገው ህይወታችን ትልቅ ትርጉም አለው፤ ዋጋው ግን የዛሬን ያህል በፍጹም አይሆንም።
0 Comments