የሃገራችን ሰው “ጽድቅ እና ኩነኔ ቢኖርም ባይኖርም ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም” ይላል ሲተርት። እውነትም ከሞት በኋላ ያለውን ህይወት አይቶ የነገረን ሰው የለም፤ መልካም ሰርታ ያረፈች ነፍስ ግን እውነተኛ እረፍትን ማግኘቷ አይቀርም። መልካምነት እና ክፋት ለእያንዳንድችን የተለያየ ትርጉም ሊኖራቸው ይችላል። በመጥፎ ነገሮች የሚተባባሩ ሰዎች አንዳቸው ለአንዳቸው መልካም እንደሆኑ ነው የሚያውቁት። እከሌ ለኔ ጥሩ ሰው ነው ብለን ስናስብ ምናልባት ጥሩነቱን የለካነው ጥቅማችንን ስላሟላልን ብቻ ሊሆን ይችላልና።
አስሩ እሾሆች የሚለው ሃሳብ የመጣልኝ፤ ከአሮጌ ተራ የገዛኋትን መጽሃፍ ሳገላብጥ ነበር። ስለመልካምነት የምትሰብከው ይህቺ የዳይላላማ መጽሃፍ የሰው ልጆችን ደስታ የሚያጠፉ፤ ውስጣዊ ሰላምን የሚረብሹ፤ በራስ ወዳድነት ወጥመድ የሚጠልፉ ከህይወታችን ነቅለን ልንጥላቸው የሚገቡንን አስር እሾሆችን በሶስት መደብ ከፍላ አቅርባቸዋልች። አካላዊ፤ አንደበታዊ እና አዕምሯዊ በማለት።
አካላዊ እሾኮች- ውጫዊ አካላችን ላይ የሚበቅሉ እሾሆች ሲሆኑ እነዚህም ሌላውን ሰው መጉዳት ወይም መግደል፤ መስረቅ እና ሴሰኝነት ናቸው።
ቃላዊ እሾኮች- አንደበታችን ላይ የሚበቅሉ እሾሆች ሲሆኑ ፤ውሸት፤ ንቀት፤ ስድብ እና ሃሜት ናቸው።
አዕምሯዊ እሾሆች ደግሞ አይምሮዋችን ላይ የሚበቅሉ እሾሆች ናቸው፤ ቅናት ወይም የሌሎችን ነገር መመኘት ፤ ክፋት እና አሉታዊ አስተሳሰቦች የአዕምሮ እሾሆች ናቸው።
ውስጣዊ ሰላም የሚጎድላት ነፍስ ምንም እንኳን ዙሪያዋ በመልካም ነገሮች ቢሞላም በእረግታ መኖርን አታውቅበትም። “ከብት ባሏለበት ኩበት ለቀማ” እንዲሉ መልካም ስራ በሌለበት መልካም ህይወት የለም። ሰላም ባልተሰበከበት ሰላም አይገኝም፤ ፍቅር ባለተዘራበት ኑሮ ፍቅር እንጨድ ማለት ቀልድ ነው። የሰው ልጅ ሁሉ ደስታን ይመኛል፤ ነገር ግን ደስታውን ለማጨድ ምን መዝራት እንዳለበት አያውቅ። ለዚህ ነው ኑሮዋችን በተለያዩ እሾሆች የተሞላችው፤ የምንዘራውን ባለማወቃችን።
በነዚህ ሶስት የህይወታችን ክፍሎች ውስጥ የሚበቅሉት እሾኮች ለኛም ሆነ ለሌሎች ሰላምን የሚሰጡ አይደሉም። አንድ በአለም የታወቀ ሰባኪ በአንድ ወቅት እንዲህ ሲል ሰምቸው ነበር ” ሰባ በመቶ የሚሆነው የሰው ልጅ በሽታ፤ ሰው በገዛ እራሱ የሚያመጣው ነው” ሲል ተናግሯል። ወደን በራሳችን ላይ ችግር እና በሽታን ባናመጣም ፤ አኗኗራችን ግን የጤናችንን እና የደስተኛንተቻንን ሁኔታ በእጅጉ ይወስነዋል። አስተሳሰባችን ደግሞ አኗኗራችንን መቅረጫ ትልቅ መሳሪያ ነው። ኑሮዋችንን በመፈተሽ እረፍት የሚነሱንን እኒህ አሾሆች አንድ በአንድ ነቅለን መጣል እንችላለን።
0 Comments