ይህ ታሪክ ታይላንድ ውስጥ የእውነት የተከሰተ ነው። ምን አልባትም ከዚህ በፊት ሰምታችሁት ሊሆን ይችላል…….በ1957 ዓ፣ም ገደማ የታይላድን መነኮሳት ገዳማቸውን ወደ ሌላ ቦታ ሲያዘዋውሩ፤ በገዳሙ ውስጥ የነበረውን ከጭቃ የተሰራ የቡድሃ ሃውልትንም ማዘዋወር ነበረባቸው። ምንም እንኳን የጭቃ ሃውልት ቢመስልም፤ ለማዘዋወር ሲሞክሩ ግን እጅግ ከባድ ሆነባቸው። ከክብደቱም የተሰነሳ ወደ መጫኛው ሲጫን መመሰንጠቅ ጀመረ…ይባስ ብሎም ዝናብ ዘነበና ጭቃውን አሟሟው። ይሄኔ መነኮሳቱ ለሃውልቱ በመጨነቅ ፤ መልሰው ወደ መሬት አስቀመጡትና ከዝናቡ ሸፍነው እስኪደርቅ አቆዩት።
መሸት ሲልም የመነኮሳቱ አለቃ፤ ሃውልቱ መድረቅ አለመድረቁን ለማየት፤ የ እጅ መብርቱን በመያዝ ወደ ሃውልቱ ተጠግቶ መብርቱን ሲያበራ፤ ከተሰነጠቀው ጭቃ ውስጥ የሚያብረቀርቅ ወርቃማ ነገር ተመለከተ። ግራ ሲገባው ጭቃውን ይበልጥ ፈለቀቀው፤ ውስጡ ያለው ወርቃማ ነገር ይበልጥ ታየ። የመነኮሳቱ አለቃ፤ የሚያየውን ማመን ተስኖት፤ ጭቃውን ከሃውልቱ ላይ ማራገፍ ጀመረ፤ ይሄኔ….ከጭቃው ሃውልት ስር ተደብቆ የነበረው እውነተኛው ከንፁህ ወርቅ የተሰራው የቡድሃ ሃውልት ቁልጭ ብሎ ታዬ። ኋላ ላይ ታሪክ አጥኒዎች ሲያስረዱ….ከብዙ መቶ አመታት በፊት ጠላት ቲቤትን የያኔዋን ሲያም ሲወሩ እና ንብረት ሲዘርፉ፤ መነኮሳቱ ይህን ሙሉ በሙሉ በወርቅ የተሰራውን የቡድሃ ሃውልት እንዳይወስዱባቸው ሲሉ፤ በጭቃ ሸፍነውት ነበር። ወራሪዎቹም ሃውልቱ በጭቃ የተሰራ ተራ ነገር ስለመሰላቸው…….ዛይዘርፉት ቀሩ። መነኮሳቱንም በሙሉ ጨፍጭፈዋቸው ስለነበር ……ሚስጥሩ እስከ ሃያኛው ክፍለ ዘመን ድረስ ሚሰጥር ሆኖ ሊቆይ ቻለ። ልብ በሉ ከንፁህ ወርቅ የተሰራውን ሃውልት ተራ ነገር……መስሏቸው…..
ይህንን ታሪክ በዙ ፀሃፊያን ከብዙ ነገር ጋር ያያይዙታል። እኔም ይህንን ታሪክ ተንተርሼ ጥቂት ነገር ማለት ፈለግኩኝ።
በእለት ተእለት ኑሮዋችን ውስጥ ከላይ ታሪኩ እንደተነገረው ሃውልቱ ጭቃ እየመሰሉን ጥለናቸው የምናልፋቸው ብዙ ወርቃማ እድሎች አሉ። ሁሉም ሰው በጭቃ የተሸፈነ የወርቅ ሃውልት ነው። እድል ስላስሰጠናቸው ብቻ ከጭቃነታቸው ባሻገር ወርቅ የሆነውን ማንነታቸውን ማየት እያቃተን፤ በህይወት መንድገድ ላይ ከብዙ ሰዎች ጋር ተላልፈናል።
በተለይ ይህ ታሪክ ፍቅርን ተራብን ለሚሉ ሰዎች ትልቅ መልዕክት ያለው ይመስለኛል……የፍቅር አጋር ሰንፈልግ፤ መስፈርታችን ምንድን ነው? ከላይ በምናየው ነገር የምንዳኛቸው ከሆነ…..በወርቅ የተሸፈነው ሃውልት ውስጡ ጭቃ፤ በጭቃ የተሸፈነው ሃውልት ደግሞ ውስጡ ወርቅ ቢሆንብንስ? ምርጫችን ስህተት የማይኖረው፤ ሰዎችን ከላይ በምናየው ነገር ብቻ መዳኘት ስናቆምነው። እውነተኛ ፍቅር የምንፈልግ ከሆነ፤ አይኖቻችን ከቅርፊቱ አልፈው መመልከት ይገባቸዋል። ቆም ብለን ብናስም ተራ ሰዎች መስለውን….ኋላ ላይ ግን ከኛ በላይ ቆመው ያየናቸው ብዙ ሰዎች አሉ፤ ከጭቃ የተሰሩ የሚመስሉ፤ ልባቸው ግን ወርቅ የሆነ ሰዎች።
በተለይ በኛ ዘመን፤ መስፈርቶቻችን እጅግ ብዙ ናቸው። በዛ ሁሉ መስፈርት ተፈትኖ የሚመሰረተው ትዳርም ሆነ ጓደኝነት ግን እምብዛም አጥጋቢ ሆኖ ሲዘልቅ አናየውም። በሌላ በኩል የኛ እናት እና አባቶች ብሎም የአያቶቻችን ትደር ያለ ምንም መስፈርት ተመስርቶ፤ እረጅም አመት ይዘልቃል? ታዲያ የቱ ላይ ነው ችግሩ፤ እኔ እንደሚመስለኝ የኛ እሩጫ ወርቅ ወደ ለበሰው ጭቃ ነው። እነሱ ግን መስፈርታቸው ሃውልቱ በለበሰው ነገር ስላልሆነ……..ቀስ በቀስ ጭቃው ሲፈርስ እውነተኛው ማንነታቸውን ይሸላለማሉ።
የሰውን ወርቅ ማንነት የሚሸፍኑ ብዙ ጭቃዎች አሉ፤ ድህነት፤ አለመማር፤ ዘር፤ መልክ….እኒህ ወርቅ ልብ ያላቸውን ሰዎች የሚሸፍኑ ጭቃዎች ናቸው። መመዘኛዎቻችን እነሱ ከሆኑ….በርግጥም ብዙ ወርቆች ተራ እየመሰሉን እናልፋቸዋል። እናም የዛሬው መልዕክቴ ይህ ነው…..በጭቃ የተሸፈኑ ብዙ የወርቅ ሃውልቶች አሉና ተራ እየመሰሉን እንዳናልፋቸው እናስተውል።
0 Comments