ይህን ታሪክ የሰማሁኝ እለት፤ እራሴን በተለየ አይን ተመለከትኩት። ወደኋላ ተመልሼ ህይወቴን ቃኘሁት፤ ምናልባት የብዙዎቻችን ኑሮ ይገልጽ ይሆናል በማለት ታሪኩን እንዲህ አሰናድቼዋለው።
ሰውየው በቤቱ አንድ ትልቅ ዛፍ ነበረው አሉ፤ ይህ ዛፍ ህልውናው እንደትንጠለጠለበት ሁላ በእጅጉ ይንከባከበው ነበር። በቀን በቀን፤ ሲመሽም ሲነጋም ወደ ዛፉ እየሄደ ምርጥ ጊዜ ያሳልፋል። ከእለታት አንድ ቀን ግን፤ ይህን ግዙፍ ዛፍ ትክ ብሎ ሲመለከተው አንዳንድ ቅጠሎቹ ቀለማቸውን እየቀየሩ እየጠወለጉ መምጣታቸውን ተመለከተ፤ ሰውየው ሃዘን ገባው። ምንም እንኳን ዛፉ ትልቅ እና ግዙፍ ቢሆንም፤ እንደምንም ከዛፉ እላይ እየወጣ፤ የጠወለጉትን ቅጠሎች በውሃ ማራሱን ተያያዘው። ተመልሰው ነፍስ እስኪዝሩ ድረስ፤ ሽቅብ ወደ ላይ እየወጣ ቅጠሎቹን እየወለወለ በውሃ ያርሳቸዋል። ለብዙ ቀን እንዲህ ሲለፋ ቆየ፤ ምንም እንኳን የተቻለውን ያህል ቢለፋም ቅጠሎቹ አንድ በአንድ ከመድረቅ እና ከመጠውለግ አልዳኑም። በመጨረሻ ሰውየው ከልፋቱ ብዛት ደከመው፤ የነበረውም ውሃ በሙሉ አለቀበት። ቀስ በቀስ ዛፉ መሞት ጀመረ……..
ይህ ሰው ሃይል እና ጉልበቱን እንዲሁም ሃብቱን በከንቱ አባከነው። የዛፉን ስር ውሃ እንደማጠጣት፤ የጠወለጉት ቅጠሎች ላይ ጊዜውን በማጥፋቱ፤ ዛፉን በሙሉ አበላሸው። ምን አልባት ብልህ ሆኖ ስሩን በውሃ ቢያርሰው ኖሮ፤ የጠወለጉት ቅጠሎች መልሰው ባበቡ፤ ሌሎችም ከመጠውለግ በዳኑ ነበር።
አብዛኛዎቻችን እንዲህ ነን፤ ህይወታችን መታደግ የሚያቅተን፤ ትኩረታችን ሁሉ፤ ስራችን ላይ ሳይሆን ቅጠላችን ላይ ስለሆነ ነው። ቅጠሎቻችን ምንድን ናቸው? ባህሪያችን፤ ልምዳችን፤ ወይም ሌሎች የአስተሳሰባችን ውጤት የሆኑ ነገሮች ሊሆኑ ይችላሉ። ስራችን ግን ማንነታችን የሚበቅልበት አስተሳሰባችን ነው። ባህሪዎቻችን ወይም ተግባሮቻችን ሲጠወልጉ፤ ስራችንን እንደማስተካከል፤ ጊዜ እና ጉልበታችንን ለውጥ በማያመጡ ነገሮች ላይ እናጠፋለን።
የሁላችንንም ቅጠል የሚያጠወልገው ነገር ይለያያል፤ አንዳንዶቻችን በሱስ እንጠወልጋለን፤ አንዳንዶቻችን በስንፍና፤ አንዳንዶቻንች በቂ ፍቅር ስለሌለን፤ አንዳንዶቻችን በራሳችን ባለመተማመናችን፤ አንዳንዶቻችን ተስፋ በማጣት፤ ብቻ በተለያይዩ ምክንያቶች መጠውለግ እንጀምራለን። መጠወለጉ ሲያንገፈግፈን እና እንደገና ለማበብ ስንወስን ደግሞ መላው ይጠፋብናል። በለፋን ቁጥር ይበልጥ እንጠወልጋለን፤ ልፋታችን ከንቱ ይሆንብናል። ምክንያቱም ብዙዎቻችን እንደ ሰውየው፤ ጊዜያችንን የምናጠፋው ለውጥ በማናገኝባቸው ነገሮች ላይ ነውና።
የሁሉም ነገር መሰረት አይምሮዋችን ነው። የጠወለገውን ክፍላችንን እንደገና ህይወት መስጠት የሚያስችለን ብቸኛው መፍትሄ አስተሳሰባችን መቀየር ብቻ ነው። እራሳችንን እንደዛፉ ብንመለከት፤ የትኛው የህይወታችን ክፍል ነው እየጠወለገ ያለው? ልፊያችንስ ከተበላሸው ባህሪያችን ማለትም ከጠውለገው ቅጠላችን ጋር ነው ? ወይስ ስር ከሆነው አስተሳሰባችን ጋር ነው?
0 Comments