ከአንድ ሰው በራፍ ላይ ቁጭ ብሎ ድንች የሚሸጥ ምሲኪን ሰው ነበረ። የቤቱ ባለቤት ሁሌም ወደ ውጪ ሲወጣ ይህንን ምስኪን ሰው ይመለከተው ነበረ። ቀኑን ሙሉ ብርድና ጸሀይ እየተፈራረቀበት ኑሮን ለማሸነፍ መድከሙ ስላሳዘነው በአቅሙ ሊረዳው ወሰነ። ነጋዴው አንዷን ድንች በ50 ሳንቲም ነበር የሚቸረችረው። ታዲያ ይህ ሰው ምስኪኑን ነጋዴ ለመርዳት በማሰብ በየቀኑ የአንድ ድንች ዋጋ እየሰጠው ለመሄድ ወሰነ። በየቀኑ 50 ሳንቲሙን እየሰጠው በአንጻሩ ምንም ድንች ሳይቀበል ይሄዳል። ከብዙ ጊዜ በኋላ ይህ ሰው እንደለመደው 50 ሳንቲሙን አኑሮለት ጉዞውን ቀጠለ። ድንገት ከኋላው “ጌታዬ” የሚል ጥሪ ይሰማል። ዞር ብሎ ሲመለከት ምስኪኑ ነጋዴ ነበር በሩጫ የደረሰበትና የጠራው።
ሰውየው በፈገግታ “ከስንት ጊዜ በኋላ ለምን በቀን በቀን 50 ሳንቲም በነጻ እየሰጠሁ እንደማልፍ ልጠይቀኝ ነው ያስቆምከኝ?” አለው
ነጋዴው ግን እያለከለከ “አይደለም ኸረ” ሲል መለሰ። ይሄኔ ሰውየው ግራ ገብቶት
“እና ለምን አስቆምከኝ?” ቢለው
“የድንች ዋጋ 75 መግባቱን ልነግርዎት ነው፤ እናም ስሙኒ ይጎድላል” አለው አሉ።
ይህንን ታሪክ የሰማሁኝ ቀን በጣም አስቆኝ ነበር። መለስ ብዬ ሳስበው ግን ከቀልድነቱ በላይ የሰው ልጅን የአልጠግብ ባይነትና ያለማመስገንን ባህሪ የሚያንጸባርቅ መስሎ ታየኝ። ሰዎች አመስጋኝ ፍጡሮች ነን ብዬ አላምንም። ልክ እንደዚህ ምስኪን ነጋዴ ነጻ በሚሰጠን ነገር ላይ እንኳን እንደራደራለን። የእኛ ባልሆነው ሀብት እንሟገታለን። በቸርነት በተሰጠን ነገር ሁሉ ይበልጥ እንጠይቃለን። ሃምሳ ሳንቲም ለምን በነጻ ተሰጠኝ ሳይሆን ለምን ስሙኒ ጎደለ የሚል አመለካከት ስላለን እኮ ነው አብዛኛዎቻችን ባለን ነገር መደሰት የሚያቅተን።
“It isn’t what you have or who you are or where you are or what you are doing that makes you happy or unhappy. It is what you think about it.”
― Dale Carnegie,
ብዙ ጊዜ ከፈጣሪ ጋርም ሆነ በየእለት ኑሮዋችን በነገሮች ላይ የምንደራደረው ልክ እንደዚህ ምስኪን ነጋዴ ነው። በነጻ የሚሰጠንን 50 ሳንቲም ሳይሆን የኑሮዋችንን ዋጋ እራሳችን ተምነን ቀሪው ጎደለ ብለን እንሟገታለን። ስዎች የሚሰጡንን ነጻ ፍቅር፤ ነጻ ክብር፤ ነጻ እምነት ዋጋ የማንሰጠው ቀሪውን ስሙኒ ስለምናስብ ነው። እኛ በባህሪያችን ነጻ የሆነን ነገር ዋጋ አንሰጠውም እንደውም አንድ ተናጋሪ ሰዎች አይምሮዋችንን በደንብ የማንጠቀምበት ነጻ ስለተሰጠን ነው ሲል ሰምቸው ግርምት ጭሮብኝ ነበር። እውነት እኮ ነው፤ የላፕቶፓችንን ያህል አይምሮዋችንን ዋጋ አንሰጠውም። ላፕቶፓችንን ቫይረስ እንዳይነካው የምንጠነቀቀውን ያህል አይምሮዋችን እንዳይበከል አንጠነቀቅም።የሚያስደንቀው ግን የሰው ልጅ በምንም ያህል ገንዘብ ሊገዛቸው የማይችላቸው ሀብቶቹ በሙሉ በነጻ የሚያገኛቸው ናቸው።
“He who is not contented with what he has, would not be contented with what he would like to have.”
― Socrates
በ50 ሳንቲሙ ያልተደሰተና ያላመሰገነ ሰው ስሙኒ ቢጨመርለት ምን ዋጋ አለው? በየቀኑ የሚቸረን 50 ሳንቲም ከበቂ በላይ ነው፤ አንዳንዴ ስሙኒው ይቀራል ብለን ሰጪውን ባናስቀይም መልካም ነበር፤ ነገር ግን ሰው ነን!!! ብዙ ጊዜ ደስታችንን የሚነጥቀን የ “ስሙኒ ይቀራል” አይነት አመለካከታችን ነው። የተሰጠንስ 50 ሳንቲም? የተሰጠን ነጻ ፍቅር፤ ነጻ ክብር፤ ነጻ እምነት፤ ነጻ ጤንነት፤ ነጻ ተስፋ? ከምንም በላይ ነጻ ህይወትስ?
ከተቻልሽ ለአዲሱ ትውልድ ስለጫት መጥፎነት ስበኪው መንግስት ከፍተኛ ቀረጥ እንዲጥልበት ጫና እናሳድር እናሳውቅ
wetatun eko bizu ngr aynun gardotal. yegaredewn mefenkel kalhone mengeru lewt yametal biyea alasbm
የሚያስተምር ቆንጆ ጽሁፍ ነው! አመሰግናለሁ
አላማችን ከግብ ለማድረስ ዉድቅና አፍራሽ ሀሳቦች አስወግደን ቆርጠን ከተነሳን በስኬት ጎዳና ላይ መጓዝ እንችላለን:: ስላበረከታችሁ ምክሪና ስላስተምራችሁና ስላሳያችሁ መንገድ ከልብ አመሰግናለሁ !!
አላማችን ከግብ ለማድረስ ዉድቅና አፍራሽ ሀሳቦች አስወግደን ቆርጠን ከተነሳን በስኬት ጎዳና ላይ መጓዝ እንችላለን:: ስላበረከታችሁ ምክሪና ስላስተምራችሁና ስላሳያችሁ መንገድ ከልብ አመሰግናለሁ !!