ብዙዎቻችን፤ በፍቅር ግንኙነታችንም ሆነ በተለያዩ ግንኙነቶቻችን ውስጥ፤ ፍቅርን ያለቦታው እናስሰዋለን፤ አለመፍለቅቂያው እንፈልገዋለን። ለዚህም ነው ፍቅር ደብዛው የጠፋ የሚመስለው። አንድ የውጪ ሃገር መምህር ይህንን ደስ በሚል ቋንቋ እንዲህ ገልጸውታል
“በአህያው ጀርባ ላይ ሆነው አህያውን እንደመፈለግ ማለት ነው” ሲሉ። ፍቅርን የምንፈልግ ሰውች ልክ አህያው ላይ ተቀምጦ አህያው ወዴት ነው ብሎ እንደሚፈልገው ሞኝ ማለት ነን። በማንኛውም የህይወታችን ግንኙነት ውስጥ ፍቅር እንደጎደለን ካስብን፤ ትክክለኛው መፍትሄ ልባችንን መመርመር ነው። ለራሳችን ፍቅር ከሌለን፤ ምንም እንኳን አለም ሁሉ ለኛ ፍቅር ቢኖረው፤ ስሜቱን መረዳት አንችልም፤ እናም ፍቅርን ፍለጋ በከንቱ እንዳክራለን።
ፍቅር ልክ እንደውሃ ምንጭ ነው፤ ከራስ ፈልቆ ሌላውን የሚያጥለቀልቅ።ፍቅር ልክ እንደጸሃይ ብርሃን ነው፤ ከልብ ፈንጥቆ ለሌላው ብርሃን የሚሆን፤ እንጂ ተመጽዋች አይደለም። ምን አልባት ፍቅር ከተራብን፤ ልባችንን ተመጽዋች አድርገነው ይሆናልና እራሳችንን እንመርምር። ማፍቀር ከባድ የሚሆንብ እኮ ለራሳችን ፍቅር ስለሌለን ነው፤ ልባችን ፍቅርን ስላልተለማመደ። ለአለም ብርሃንን መስጠት፤ ለጸሃይ ስራዋ አይደለም፤ አያለፋትም፤ ምክንያቱም ተፈጥሮዋ ነውና። እኛም በውስጣችንን ፍቅርን ከኮተኮትነው፤ አለምን ሁሉ መውደድ ልፋት አይሆንብም፤ ሳናውቀው ፍቅር ከኛ ወደሌላው እንደጨረር ይፈነጥቃል እንጂ…..ልክ እንደ ጸሃይ ብርሃን።
የፍቅርም ምንጩ እኛው እራሳችን ሆነን ሳለን……ፍቅርን የማያፈልቅ ሌላ ጉድጓድ ስንቆፍር፤ ጅንበራችን እንዳትጠልቅ።
0 Comments